የኢትዮ ቴሌኮም መሰረታዊ ሰራተኛ ማህበር አመራሮች ወቅታዊ ጉዳይ በሆነው የኢትዮ ቴሌኮም ወደ ግል የማዘዋወር የመንግስት ውሳኔን ተከትሎ አመራሮች በሰራተኞች ቀጣይ ሁኔታዎች ላይ እና አጠቃላይ ከጉዳዩ ጋር በተገናኘ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ምሁራን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት የስልጠናና የምክክር መድረክ ጥቅምት 7 እና 8 2012 ዓ.ም በኢትዮ ቴሌኮም የስልጠና ማዕከል/TExA ውስጥ ተደርጓዋል፡፡ በስልጠናው ወቅት የማህበሩ ሊ/መንበር አቶ ካሳሁን ሰቦቃ ለእንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁ በማለት በዚህ የመንግስት ውሳኔ ውስጥ የማህበሩ አመራሮች ሊኖራቸው ስለሚገባ ሚናና ሰራተኞች ስለሚጠበቅባቸው ቅድመ ዝግጅት በተመለከተ የአደራ መልዕክት አስተላልፈው የስልጠናውና የምክክር መድረኩ አመራሮች ስለ ጉዳዩ የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ለማስቻል ታስቦ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ በመቀጠል የአ.አ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስና ቢዝነስ ዲፓርትመንት ዲን የሆኑት ዶ/ር ዘርአየሁ ስሜ ይህንን መድረክ ከዩኒቨርሲቲው ጋር በትብብር መዘጋጀቱ አመስግነው መሰል ማህበራት ከምሁራን ጋር በትብብር መስራታቸው ሊያገኙት ስለሚችሉት ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች ገልፀው ማህበሩ ስለወሰደው ተነሳሽነት አድናቆታቸውን ችረዋል፡፡ በስልጠናውም የተሳተፉት የዲፓርትመንቱ ምሁራን ከርዕሱ ጋር በተገናኘ ሰፊ እውቀትና ጥልቅ ጥናት ያካሄዱ መሆናቸውና በአፍሪካ ደረጃ ያሉትን ተመሳሳይ ተሞክሮዎችን በመገምገም ከሀገራችን ሁኔታዎች ጋር በማዛመድ ያላቸውን እውቀትና ልምድ እንደሚያካፍሉ ገልጸው አመራሮች ስልጠናውን በንቃት እንዲሳተፉ አሳስበዋል፡፡
የስልጠናው ርዕሶች ከጉዳዩ ተዛማጅ የሆኑና ወደግል በማዘዋወር ሂደት ውስጥ የማህበሩ አመራሮች ለሚኖራቸው የህግ ግንዛቤ ከፍ ለማድረግ የተዘጋጁ ሲሆኑ እነዚህም፡-
- የኢትዮጵያ ዐብይ-ኢኮኖሚ (ማክሮ-ኢኮኖሚ) ሁኔታና መንግስት በኢኮኖሚ ዉስጥ (የመንግስት ተቋማትን ወደ ግል ማዞርን ጨምሮ) የሚኖረው ሚና
- የመንግስትን ተቋማትን ወደ ግል በማዞር ውስጥ በአፍሪካ ያለው ተሞክሮ
- የቴሌኮም ሴክተርን ወደ ግል በማዞር ሂደት ላይ ያለው አለም አቀፋዊና አህጉራዊ ተሞክሮ
- ኢትዮ ቴሌኮምን ወደ ግል በሚዞርበት ወቅት የሚኖሩት መልካም አጋጣሚዎችና ተግዳሮቶችናበኢትዮጵያ የመንግስት ተቋማትን ወደ ግል በማዞር ሂደት ላይ ያሉት የህግና የፖሊሲ ማዕቀፎች